የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን ሥልጣንና ተግባር ከፌዴሬሽን ምክር ቤት ሥልጣንና ተግባር እንደማይጣረስ ተገለፀ

የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የፌዴሬሽን ምክር ቤትና የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን በኢ.ፌ.ዲ.ሪ በፌዴሬሽን ምክር ቤት ተገኝተው ውይይት አካሂደዋል፡፡ የጋራ መግባቢያ ሰነድም ተፈራረመዋል፡፡ 
ውይይቱን በንግግር የከፈቱት የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ የተከበሩ አቶ አደም ፋራህ  ሲሆኑ በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ-መንግስት አንቀፅ 62 ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ተለይተው በተሰጡት ሥልጣንና ተግባር መሠረት ምክር ቤቱ የማንነት፣ የአስተዳደር ወሰንና ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄዎች እንዲሁም የሕገ መንግሥት ትርጉም ጉዳዮች ሲቀርቡለት የመጨረሻ ሕገመንግሥታዊ ውሳኔ እንደሚሰጥ ገልፀው ከዚህ አንጻርም የአስተዳደር ወሰንና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን በአዋጅ ሲቋቋም በአንዳንድ ወገኖች ሕገመንግሥትን እንደሚጥስ፣  የፌዴሬሽን ምክር ቤትንና የክልሎችን ሕገ መንግሥታዊ ሥልጣንና ተግባራትን እንደሚጋፋ ተቆጥሮ ወደ ምክር ቤት ቀርቦ በመጨረሻም ምክር ቤቱ ምንም ዓይነት የሕገመንግሥት ጥሰትም ሆነ የምክር ቤቱንና የክልሎችን  ሥልጣንና ተግባራትን እንደማይጋፋ በማረጋገጥ ኮሚሽኑ በአዋጅ እንዲፀድቅ መወሰኑን ገልፀዋል፡፡  
ስለሆነም የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን በማቋቋሚያ አዋጁ መሠረት የወሰን፣ የማንነትና ራስን በራስ የማስተዳደር ጉዳዮች ሲቀርቡ ሳይንሳዊ ጥናትና ምርምር በማድረግ በመጨረሻ ግኝት ላይ ተሞርክዞ ለውሳኔ የሚረዳውን ሳይንሳዊ ምክረ ሀሳብ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት እንደሚያቀርብና ድጋፍ እንደሚያደርግ አዋጁን ጠቅሰው አብራርተዋል፡፡  
ከዚህ ውጪ የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮችን በተመለከተ ምንም ዓይነት ውሳኔ እንደማያስተላልፍና የመጨረሻን ውሳኔ የመስጠት ሥልጣን የፌዴሬሽን ምክር ቤት ብቻ መሆኑን አፈጉባዔው አስረግጠው አስረድተዋል፡፡ ከዚህ በመነሳት ኮሚሽኑን በተመለከተ  ዜጎች ከብዥታ በጸዳ ሁኔታ የጠራ ግንዛቤ እንዲይዙም አሳስበዋል፡፡     
ኮሚሽኑ የቀጣይ ሦስት ዓመት ስትራተጂክ ዕቅድ ነድፎ ወደ ተግባር ሥራ መግባቱን የኮሚሽኑ ኮሚሽነር ዶ/ር ጣሰው ገብሬ ገልፀዋል፡፡ ከምክር ቤቱ ጋር በትብብርና በጋራ ለመስራት በተዘጋጀው የመግባቢያና 
የትብብር ሰነድ ላይ ውይይት ከተደረገ በኋላ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ እና የኮሚሽኑ ሰብሳቢ ዶ/ር ጣሰው ገብሬ ተፈራርመዋል፡፡ 
ሰኞ ሐምሌ 13/2012ዓ.ም